ከጁንዱብ ቢን ዐብደላህ አልቀስሪይ -አላህ መልካም ስራቸውን ይውደድላቸውና- እንደተላለፈው እንዲህ አሉ: የአላህ መልክተኛ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም እንዲህ አሉ: "የሱብሒን ሶላት የሰገደ ሰው በአላህ ከለላ ስር ነው። ከናንተ አንዳችሁ በአላህ ጥበቃ ስር ያለውን ሰው በምንም መንገድ አይጉዳ። ያንን የሠራ ሰው የአላህ ቁጣ በእርግጥ ይይዘዋል ከዚያም በአፍጢሙ በጀሀነም እሳት ውስጥ ይደፋዋል።" ሶሒሕ ነው። - ሙስሊም ዘግበውታል።
explain-icon

ትንታኔ

ነቢዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም የፈጅርን ሶላት የሰገደ ሰው በአላህ ጥበቃና ከለላ ስር ስላለ እንደሚከላከልለትና እንደሚረዳው ተናገሩ። ከዚያም ነቢዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም የፈጅርን ሶላት በመተው ወይም ሰጋጁን በመተናኮልና ሰጋጁ ላይ ወሰን በማለፍ ይህንን ከለላ ከማፍረስ አስጠነቀቁ። ይህንን የፈፀመም ይህንን ጥበቃ ስለጣሰ ለብርቱ ዛቻ የተጋለጠ ይሆናል። የአላህን ሀቅ ወሰን ስላለፈም በአላህ ይፈለጋል። አላህም የሚፈልገውን ያገኘዋል፤ ከዚያም በአፍጢሙ እሳት ውስጥ ይደፋዋል።

explain-icon

ከሐዲሱ የምንጠቀማቸው ቁምነገሮች

  • የፈጅር ሶላት አንገብጋቢነትና ትሩፋቷ መገለፁን እንረዳለን።
  • ፈጅር የሰገደን ሰው በሚተናኮል ላይ ብርቱ ማስጠንቀቂያ መምጣቱን እንረዳለን።
  • አላህ ደጋግ ባሮቹን የሚተናኮል ሰውን እንደሚበቀል ተረድተናል።