ከዐብደላህ ቢን መስዑድ ረዲየሏሁ ዓንሁ -አላህ መልካም ስራቸውን ይውደድለላቸውና- እንደተላለፈው እንዲህ አሉ: «የአላህ መልክተኛ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም -የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና- እንዲህ ብለዋል: "የሙስሊምን ሰው ገንዘብ ለመውሰድ እየዋሸ የማለ ሰው አላህ በርሱ ላይ የተቆጣበት ሆኖ ይገናኛል።" አሽዓሥም እንዲህ አለ: "በአላህ እምላለሁ! ይህንን የተናገሩት በኔ ምክንያት ነበር። በኔና በአንድ አይሁድ መካከል የመሬት ውል ነበረንና ካደኝ። ነቢዩ ሶለሏሁ ዐለይሂ ወሰለም -የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና- ዘንድም ለፍርድ አቆምኩት። የአላህ መልክተኛም ሶለሏሁ ዐለይሂ ወሰለም -የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና- "ማስረጃ አለህን?" አሉኝ። እኔም "የለኝም።" አልኩኝ። ከዛም ለአይሁዱ "ማል።" አሉት። እኔም "የአላህ መልክተኛ ሆይ! እንዲህ ከሆነማ ምሎ ገንዘቤን ይወስዳል።" አልኳቸው። አላህም {እነዚያ በአላህ ቃል ኪዳንና በመሐላዎቻቸው ጥቂትን ዋጋ የሚለውጡ ... } ሙሉ አንቀፁን አወረደ።"» ሶሒሕ ነው። - ቡኻሪና ሙስሊም ዘግበውታል።
explain-icon

ትንታኔ

ነቢዩ ሶለሏሁ ዐለይሂ ወሰለም -የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና- የሚምለው ሰው ውሸቱን እንደሆነ እያወቀ በመሃላው የሌላን ሰው ገንዘብ ለመውሰድ በአላህ መማልን አስጠነቀቁ። ይህ ሰውም አላህ የተቆጣበት ሆኖ ይገናኛል። አሽዓሥ ቢን ቀይስም ረዲየሏሁ ዐንሁ የዚህን ንግግር ሰበብ ሲገልፅ እንዲህ አለ: ነቢዩ ሶለሏሁ ዐለይሂ ወሰለም ይህንን የተናገሩት በኔና በአንድ አይሁድ ሰውዬ መካከል በመሬት ባለቤትነት ጉዳይ ጭቅጭቅ ስለነበረን ነው። ወደ ነቢዩም ሶለሏሁ ዐለይሂ ወሰለም -የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና- ለመፋረድ ሄድን። ለአሽዓሥም እንዲህ አሉት: "የከሰስከው ነገር ላንተ እንዲፈረድ ማስረጃ ማምጣት አለብህ። ይህንን ካልቻልክ የከሰስከው ተከሳሽህ መሃላው ካልያዘው በቀር ላንተ ምንም መብት የለህም።" አሽዓሥም እንዲህ አለ: "የአላህ መልክተኛ ሆይ! እንዲህ ከሆነማ ይህ አይሁድ ሰውዬ ምንም ሳይገደው ምሎ ገንዘቤን ይወስዳል።" አላህም ይህንን ንግግር በቁርአን ለማረጋገጥ ይህንን አወረደ: {እነዚያ በአላህ ቃል ኪዳን የሚለውጡ} ትእዛዙ አማኞች አደራን እንዲወጡ እያዘዘ ነው። {በመሃሎቻቸውም (የሚለውጡ)} በውሸት በስሙ የሚምሉ {ጥቂትን ዋጋ} የዱንያን ስብርባሪ ለማግኘት {እነዚያ በመጨረሻይቱ ዓለም ምንም ዕድል የላቸውም።} ምንም ዕጣ የላቸውም። {በትንሳኤ ቀንም አላህ አያነጋግራቸውም።} የሚያስደስታቸውንና የሚጠቅማቸውን ንግግር አያናግራቸውም። ይልቁንም ይቆጣባቸዋል። {የትንሳኤ ቀን ወደነርሱ አይመለከትም።} የእዝነትና የበጎነት እይታን አይመለከታቸውም። {አያነፃቸውምም።} በመልካም እያወሳ አያነፃቸውም። ከወንጀልና ከርክሰትም በምህረቱ አያጠራቸውም። {ለነርሱም አሳማሚ ቅጣት አላቸው።} በፈፀሙት ወንጀል ምክንያት አሳማሚ ቅጣት አላቸው።

explain-icon

ከሐዲሱ የምንጠቀማቸው ቁምነገሮች

  • የሰዎችን ገንዘብ በውሸት መጠቀም ክልክል መሆኑን እንረዳለን።
  • የሙስሊም ሐቅ አነሰም በዛም ከባድ መሆኑን እንረዳለን።
  • ማስረጃ ማምጣት የሚጠበቅበት ከሳሽ ሲሆን መሀላ የሚጠበቅበት ደግሞ ክሱን ያስተባበለው ተከሳሽ ነው።
  • እውነት የሚረጋገጠው በምስክሮች ነው። ከሳሽ ማስረጃ ካላገኘ ግን ተከሳሽ መማል ይጠበቅበታል።
  • የውሸት መሃላ (የሚን አልጘሙስ) ክልክል መሆኑን እንረዳለን። (የሚን አልጘሙስ) ማለት ማዩ የሌላን ሰው ሐቅ ለመውሰድ በውሸት የሚምለው መሃላ ነው። ይህም ሰውዬውን ለአላህ ቁጣና ቅጣት የሚያጋልጥ ከትላልቅ ወንጀል የሚመደብ ነው።
  • ዳኛ ለተካሳሾች መምከር እንደሚገባው እንረዳለን። በተለይ ደግሞ ከተከሳሾች መሃላ በሚያስፈልግበት ወቅት መምከር ይገባዋል።