ነቢዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና) ሁሉም አማኝ የትንሳኤ ቀን ብቻውን አላህ ፊት እንደሚቆምና አላህም ማንም በመካከላቸው ንግግሩን የሚተረጉም አስተርጓሚ ሳይኖር እንደሚያናግረው ተናገሩ። ከፊት ለፊቱ ካለችው እሳት ለመዳን የሚሄድበት መንገድ ያገኝ እንደሁ በሚል በድንጋጤ ብዛት ወደ ግራና ቀኝ አቅጣጫ እንደሚመለከትም ተናገሩ። ወደ ቀኝ አቅጣጫ ሲመለከትም ካሳለፈው መልካም ስራ በቀር ሌላ ምንም አይመለከትም። ወደ ግራ አቅጣጫ ሲመለከትም ካሳለፈው መጥፎ ስራ በቀር ሌላ ምንም አይመለከትም። ከፊትለፊቱ ሲመለከትም ከእሳት በቀር ሌላ ምንም አይመለከትም። በሲራጥ ላይ ማለፍ የግዱ ስለሆነበት እሳትን ወደ ጎን አድርጎ መተውም አልተቻለውም። ቀጥለውም ነቢዩ (የአላህ ሰላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና) የተምር ክፋይን የምታህል ትንሽ ነገር እንኳ በመመፅወት በናንተና በእሳት መካከል የሚከልል የመልካም ስራና የምፅዋት ጋሻ አዘጋጁ አሉ።