ኢብኑ ዑመር (ረዲየሏሁ ዐንሁማ) - አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና - እንዳወሱት ነቢዩ (ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም) የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና ትከሻውን ያዙና እንዲህ አሉት: በዱንያ ውስጥ ስትኖር ከፈጣሪ ጋር ከመጠመድ ያዘናጉ ከነበሩ ግንኙነቶች፣ ከቤተሰቡና ከዘመዱ ተገልሎ የሚያስጠጋው ቤት ወደሌለበትና የሚጠብቀው ነዋሪ ወደሌለበት ሀገር እንደገባ እንግዳ ሁን፤ እንደውም ከእንግዳም የባሰ ሁን። ይኸውም ሀገሩን ፍለጋ በመንገድ እንደሚያልፍ መሆን ነው። ምክንያቱም እንግዳ የሆነ ሰው ሀገሩ መግባት አስቦ መንገድ ከጀመረው ሰው በተቃራኒ በእንግድነት ባረፈበት ሀገር ተረጋግቶ ይቀመጣልም ያሳልፋልም። የመንገድ ተጓዥ ባህሪ ግን ነገሮችን ማቅለል፣ መጓዝን አለመተውና ወደ ሀገሩ ለመድረስ በጉጉት መጣር ነው። ተጓዥ የሆነ ሰው ሀገሩ ከሚያደርሰው ነገሮች ውጪ ተጨማሪ ነገር እንደማይፈልገው ሁሉ ልክ እንደዚሁ አንድ አማኝ በዱንያ ውስጥ ሲኖር ወደ አላማው ስፍራ ከሚያደርሰው ነገር ውጪ ተጨማሪ ነገሮችን አይፈልግም። ኢብኑ ዑመርም ይህን ምክር በመመርኮዝ እንዲህ ይል ነበር: ያነጋህ ጊዜ ምሽትን አትጠብቅ፤ ያመሸህ ጊዜ ንጋትን አትጠብቅ፤ ነፍስህን የቀብር ነዋሪ አድርገህ ቁጠራት፤ እድሜ ከጤናና በሽታ አያገልምና። ለበሽታ ዘመንህ ስንቅ ሊሆንህ ዘንድ የጤንነትህን ዘመን በአምልኮ ተቻኮልባት፤ ባንተና በጤንነት መካከል በሽታ ከመጋረዱ በፊት በጤንነት ዘመንህ መልካም ስራዎችን ሸምት፤ የዱንያ ህይወትህን ሸምትባት፤ ከሞት በኋላ የሚጠቅምህን ነገር ዱኒያ ላይ ሳለህ ሰብስብ!