ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና) ዓማር ቢን ያሲርን (ረዲየሏሁ ዐንሁ) - አላህ መልካም ሥራቸውን ይውደድላቸውና - ለሆነ ጉዳይ ጉዞ ላኩት። በግንኙነት ወይም በተኛበት በስሜት የዘር ፈሳሽ በመውጣቱ ምክንያት ጀናባ አገኘው። የሚታጠብበት ውሃም አላገኘም። የሚያውቀው ዉዱእ ሲያጠፋ ለትንሹ ሐደሥ የሚደረገውን የተየሙም ብይን እንጂ ጀናባ ሲያጋጥም የሚደረገውን የተየሙም ብይን አያውቅም ነበር። ስለ አፈፃፀሙ ከተመራመረ በኋላ ዉዱእ ሲጠፋ የምድር ገፅ ላይ በሚገኝ አፈር ከፊል የዉዱእ አካላትን እንደሚታበሰው ለጀናባ የሚደረገው የተየሙም አፈፃፀም ደግሞ የግድ መላ ሰውነትን በአፈር ማዳረስ መሆን አለበት ብሎ አሰበ። ይህም በውሃ ቀይሶት ነው። ሰውነቱን ባጠቃላይ እንዲነካም አፈር ላይ ተንከባለለና ሰገደ። ወደ ነቢዩ (የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና) የመጣ ጊዜም ትክክል ነው የፈፀምኩት ወይስ አይደለም? የሚለውን ለማወቅ ያደረገውን አወሳላቸው። ነቢዩም (የአላህ ሶላትና ሰላም በእርሳቸው ላይ ይስፈንና) ከሁለቱም ሐደሦች ማለት እንደሽንት ካለው ዉዱእ የሚያጠፋው ትንሹ ሐደሥ እና እንደ ጀናባ ካለው ገላ የሚያስታጥበው ትልቁ ሐደሥ የአፀዳድ አፈፃፀምን ገለፁለት። እርሱም በሁለት እጆቹ አንድ ጊዜ አፈርን በመምታት ከዚያም በግራ እጁ ቀኝ እጁን ያብሳል፤ የመዳፎቹን የላይኛውን ክፍልና ፊቱን ያብሳል።